ቅድስት ድንግል ማርያም

ቅድስት ድንግል ማርያም
ምስለ ፍቁር ወልዳ

Thursday, February 23, 2012

ለየካቲት ኪዳነ ምሕረት ቅዳሴ በኦፕፊኮን/ዙሪክ ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን















በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::
የዙሪክ (ኦፕፊኮን) ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ዕሑድ የካቲት 18 ቀን 2004 ዓ.ም (26.2.2012) የኪዳነ ምሕረትን ዓመታዊ በዓል የቅዳሴ ሥነ-ሥርዓትና ልዩ ልዩ መንፈሳዊ መርሃ ግብር የሚኖር መሆኑን በትሕትና እንገልጻለን:: ላልሰሙ አሰምታችሁ ሁላችንም የበረከቱ ተሳታፊዎች ለመሆን በሰላም ያገናኘን!
የሰበካ ጉባኤው

Thursday, February 16, 2012

ከ "ፍኖተ ጽድቅ" የዙሪክ ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን 10ኛ ዓመት ዕትም የተወሰደ:: መልዕክት

እስመ ኢይገድፎ እግዚአብሔር ለሕዝቡ፤ እስመ ውስተ እዴሁ ኲሉ አጽናፈ ምድር
እግዚአብሔር ሕዝቡን አይጥላቸውም፤የምድር ዳርቻወችም በእጁ ውስጥ ናቸው
መዝ :94፣4




ማእምረ ኅቡአት የሆነ እግዚአብሔር የቀደመውን ሰው በአርአያውና በአምሳሉ ሲፈጥረው ምን ሊያደርግና ምን ሊሆን እንዲሚችል ሳያውቀው ቀርቶ አልነበረም፤ ይልቁንም ሁለት አበይት የሆኑ ሀብታትን ሰጥቶ አከበርው እንጂ፤ እነርሱም 1ኛ፦ የሚያስተውልበትን እውቀት፤ 2ኛ፦ ሙሉ ነፃነት ናቸው ዘዳግም 30፣19 ነገር ግን በገነት በደስታ የመኖር እድል ተስጥቶት የነበረው ሰው እነዚህን ክቡር የሆኑ የእግዚአብሔር ስጦታዎችን በአግባቡ ሊጠቀምባቸው አልቻለም። ይባስ ብሎ ማስተዋልን ለክፉ ምኞት፤ ነፃነቱንም ለጥፋትና ለውርደት ተጠቀመበት መዝ ዳዊት 48፤12። « ሰብእሰ እንዘ ክቡር ውእቱ ኢያእመረ ወኮነ ከመ እንስሳ ዘአልቦ ልብ ወተመሰሎሙ » ሰው ግን ክቡር ሆኖ ሳለ አያውቅም እንድሚጠፉ እንስሶች መሰለ ይላል። በመሰረቱ አዳም በነጻነቱ ምክንያት በራሱ ላይ ላደረሰው ችግር ሁሉ ተጠያቂው ነጻነቱን የሰጠው እግዚአብሔር ሳይሆን በነፃነቱ ያልተጠቀመው አዳም ነው። የሆነው ሆኖ እግዚአብሔር ሕዝቡን አይጥልም ርስቱንም አይተውምና መዝ፡93፤14 በህገ ልቦና ያመልኩት የነበሩትን ህገ ኦሪት ፤በመጨርሻም ወርዶ ተወልዶ ህገ ወንጌልን በመስጠት በነፃነታችን ምክንያት ያመጣነውን ችግር በቀራንዮ አደባባይ እራሱን አሳልፎ በመስጠት አሰወገደልን።ኢሳ 53፤4 ገላትያ 5፤1

ከዚህ በኋላ ያለው አዲሱ የሰው ልጅ ሕይወት እና ታሪክ ሰው ከሆነው አምላክ ጋር ያለው ግንኙነት እጅግ የጠበቀና ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱና ወንጌልን አስተምሩ ማቴ፤28፤19 ባላቸው ደቀመዛሙርቱ ምክንያት ይህን ዓለም ጨለማ የነበርው ብርሃን፤ ጠማማ የነበረው ቀና፤ ጐምዛዛ የነበረው ጣፋጭ፤ አላዋቂ የነበረው አዋቂ፤ በተስፋ መቁረጥ ውስጥ የነበርው ባለተስፋ፤ ካጋንንት ባርነት ወደ እግዚአብሔር ልጅነት የተመለሰ ሆነ። መዝ.106፤13-15 በመቀጠልም በቅዱስ እስጢፋኖስ ሞት ምክንያት በኢየሩሳሌም ባለችው ቤተክርስቲያን ላይ ታላቅ ስደት በመሆኑ የሐዋ ሥራ 8፤1 ከኢየሩሳሌም ውጭ የመጀመሪያው ቤተ ክርስቲያን በአንፆኪያ ተመሰረተች። የሐዋ ሥራ 11፤26

ሀገራችን ኢትዮጵያም በ34ዓ.ም. በጃንደረባው አማካይነት የክርስትና እምነት፤እንዲሁም በ4ኛው ክፍለ ዘመን መጀምሪያ ደግሞ በከሳቴ ብርሃን አባ ሰላማ የወንጌል ትምህርትና የቤተክርስቲያን ስርዓት ተጠቃሚ በመሆኗ ላለፉት 2000 ዓመታት ታሪኳን፤ ባህሏንና ትውፊቷን በክርስትና ሀይማኖት ላይ መሰረት ያደረገችው ኢትዮጵያ ከቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት ጋር ያለው አንደነቷ ጸንቶ ቆይቷል። ለወደፊቱም ቀጣይነት እንዲኖረው የአዲሱ ትውልድ ሃላፊነት ነው።
«ግነዩ ለእግዚአብሔር ወጸውዑ ስሞ ወንግርዎሙ ለአሕዛብ ምግባሮ » እግዚአብሔርን አመስግኑ ስሙንም ጥሩ ለአሕዛብም ሥራውን ንገሩ መዝሙር 104፤1 እንዳለው ቅዱስ ዳዊት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ከሀገር ውጭ ይህንን የካበተ መንፈሳዊ ሀብቷን ለማዳረስ ጥረት ማድረግ ከጀመረች ግማሽ ምዕተ አመት በላይ አስቆጥራለች። ከላይ በርእሱ እንደተጠቀሰው መዝሙር 94፤4 እኛም ከአገራችን በብዙ ሺህ ኪሎሜትር ርቀን ብንገኝም በዚህ በስዊዘርላንድ ሀገር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን መንፈሳዊ ግልጋሎቷንና ቡራኬዋን መስጠት ከጀመረች ከ30 ዓመታት በላይ የሆናት ሲሆን በዙሪክ ከተማ በእናታችን በቅድስት ድንግል ማሪያም ስም በተሰየመ ቤተክርስቲያን ሙሉ መንፈሳዊ አገልግሎት መስጠት ከተጀመረ ግን እነሆ ዛሬ 10 ዓመታችንን ሞልተናል። ስለአደረገልን ሁሉ « ይትባረክ እግዚአብሔር አምልከ አበዊነ » ያባቶቻችን አምልክ እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን እንላለን።
በመጨርሻም የዙሪክ ደብረ ገነት ቅድስት ማሪያም ቤተክርስቲያን ለልጆቿ « ንዑ ንትፈሣሕ በእግዚአብሔር። ወንየብብ ለአምላክነ ወመድኃኒነ። ወንብፃ ቅደመ ገጹ በአሚን ።ወበመዝሙር ንየብብ ሎቱ እስመ አብይ ውእቱ እግዚአብሔር አምላክነ። »
ኑ በእግዚአብሔር ደስ ይበለን ፤በአምላክ ለመድኃኒታችን እልል እንበል ፤በምስጋና ወደፊት እንድረስ በዝማሬም ለእርሱ እልል እንበል ፤እግዚአብሔር ታላቅ አምላክ ነውና ። መዝ.94፤1-3 በማለት ጥሪዋን ታስተላልፋለች።
ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር ::
መልአከ ገነት አባ ኃ/ጊዮርጊስ ወ/ማርያም (ቆሞስ) በስዊዘርላንድ የኢ/ኦ/ተ/ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ

Thursday, February 9, 2012

ቅዳሴ ዕሑድ የካቲት 4 ቀን / 12.Februar 2012

ዕሑድ የካቲት 11 ቀን (February 19. 2012) በዙሪክ ደብረ ገነት ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስትያን እንደተለመደው መደበኛ መርሃ ግብር የሚኖር መሆኑን የሰበካ ጉባኤው በትህትና ያስታውቃል:: አድራሻውን ለGPS ተጠቃሚዎች - Wallisellerstrasse 20, 8152 Glattbrugg or Opfikon መስጠት ይቻላል::

Thursday, February 2, 2012

ዳግመኛ ፍጠረን! - ግጥም (ነሐሴ 2002 - ደብረ ገነት ቅድስት ድንግል ማርያም ኦፕፊኮን/ ዙሪክ 10ኛ ዓመት -ልዩ እትም ) የተወሰደ

ዳግመኛ ፍጠረን
"እግዚአብሔርም አለ: ሰውን በመልካችንና በአምሳላችን እንፍጠር" ኦ.ዘ.ፍ. 1:26
ቸሩ እግዚአብሔር ፈጣሪ አባታችን
ቢወደን ቢያከብረን ባምሳሉ ፈጠረን
ከቶ እንዳይቸግረን ምንም እንዳይጎድለን
ብዙ ተባዙባት..
ምድርንም ግዙ ብሎ አስረከበን::
ታናሽ ለታላቁ ታዛዥ እንዲሆነው
ታላቁም ታናሹን ከልቡ እንዲወደው
ዘር ቀለም ሃይማኖት ጥቅም ሳይለውጠው
ተፋቅሮ እንዲኖር ሕሊና ቢሰጠው
ምነው ያምላክ ፍጡር መንገዱ ቸገረው?!
"እግዚአብሔርም ሰዎችን በመፍጠሩና በምድር ላይ እንዲኖሩ በማድረጉ አዘነ: እጅግም ተጸጸተ" ኦ.ዘ.ፍ. 6:5
ለምንስ አያዝን ለምን አይጸጽተው
እሱ እየቀረበን እኛ ስንርቀው
ለቅድስና ፈጥሮን እኛ ስናረክሰው
ተፋቀሩ ሲለን እኛ እየተባላን
ደግ ስሩ ሲለን እኛ እየከፋን
መልካም ፍሬ ተክሎ እጸ በለስ ሲያምረን
ስለምን አያዝን ለምን አይጸጽተው?
ቃየሎች ሲበዙ አቤሎች መንምነው
ለምን አይቆጣ አያስደነግጠው?
አንድ አርጎ ሲፈጥረን እሱ ሳይሰለቸው
የሰው ልጅ መለየት መበታተን ሲያምረው
የሌላው የሌላው የውጭው ሳያንሰው
ደጀ ሰላም ገብቶ ይኽ ክፉ በሽታው
እኚህ አባት ከየት? እኛስ ከየት ናቸው?
ማወቅ ያዳግታል ካነጋገራቸው
ሲዳሞ-ወለጋ-ጉራጌ -ሐረሬ
ጎንደር ወይስ ጎጃም ይሆኑ እንደ ትግሬ?
የት ነው ሀገራቸው? ምንድነው ቋንቋቸው?
ብሎ ሲከፍላቸው
ቃሉን እንዲሰብኩ እሱ ለሾማቸው
ቢያጠፉ ቢያለሙ እሱ ፍርድ እያለው
የሰው ልጅ ዳኝነት ስለምን አማረው?
ካይኑ ውስጥ ምሰሶ ማውጣት ሳይቻለው
የሌላውን ጉድፍ ከቶ በምን አየው?
ከፈጣሪው ቀድሞ መፍጠር ሲከጅለው
እንዴት አይቸገር እንዴት አይጸጽተው!

አንደኛው ሲተጋ ለጽድቅ ለነፍሱ
የጌታ ማደርያ ሲገነባ ዳሱ
ትርጉሙ ምንድነው ሌላኛው ማፍረሱ
ይሄ ይሆን እንዴ
ትንቢቱ ሊፈጸም ሰዓቱ መድረሱ?!
እግዚኦ ፈጣሪ
በዚች አጭር እድሜ ስንቱን አሳየኽን
ስንቱን አስተማርከን በስንቱስ ፈተንከን
ባክህ ተለመነን ባክህ ይቅር በለን
እንደ ቸርነትህ በይቅርታህ ጎብኘን
እንደ ኖህ ከጥፋት በጀልባህ አትርፈን
ከቁጣ አድነህ እባክህ ለውጠን
ስልጣን አለህና ዳግመኛ ፍጠረን::
ከማክዳ በቀለ

ቃለ መጠይቅ - ከ "በስዊዘርላንድ የደብረ ገነት ቅድስት ማርያም 10 ዓመት ክብረ በዓል ልዩ እትም" የተወሰደ

ቃለ መጠይቅ


ስዊዘርላንድ የደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የተመሰረተችበት 10ኛ ዓመትን ለማክበር በመዘጋጀት ላይ እንገኛለን:: ቤተ ክርስቲያኒቱ እንዴት እና በእነማን ተመሰረተች? ማን ያውራ የነበረ ማን ያርዳ የቀበረ እንዲሉ እንዲያስረዳን ለቃለ ምልልስ የጋበዝነው አቶ ምሥጢረ ኃይለ ሥላሴን ነው::አቶ ምሥጢረ ከምስረታው ጀምሮ እስካሁን ድረስ በሰበካ ጉባኤው ውስጥ በተለያዩ ሃላፊነቶች ላይ ሲያገለግል የቆየና በአሁኑም (አዲሱ)የሰበካ ጉባኤ የውጭ ግንኙነት ሃላፊ ነው::
ከአቶ ምሥጢረ ጋር ቆይታ አድርገው ቃለ ምልልሱን ያጠናቀሩት በቃሉ ተገኘወርቅና ሰሎሞን ረታ ናቸው::

ጥያቄ: የደብረ ገነት ቅድስት ማርያም እንዴት ተመሰረተች? በእነማን ተመሰረተች?
አቶ ምሥጢረ: ቀደም ሲል እ.አ.አ 1999 ዓ.ም.(በዚህ ቃለ መጠይቅ ውስጥ ቀናቱ በሙሉ እንደ አውሮፓውያን ዘመን አቆጣጠር የተሰጡ ናቸው) በበጋው ወር ልጃችን ማረንን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነትና ስርዓት ክርስትና ለማስነሳት ከነበሩን አማራጮች መካከል አንዱ ጄኔቫ የሚቀጥለውን የቅዳሴ ወቅት መጠበቅ (በዚያን ጊዜ ጄኔቫ የሚቀደሰው በዓመት ከሶስት ጊዜ ባልበለጠ ከበለጠም በአጋጣሚ ካህን ለስብሰባ ከመጣ ዲያቆን ከእንግሊዝ አገር ወይም ከኢየሩሳሌም በማስመጣት ነበር)ስለሆነም ወንድ ልጅ በአርባ ቀኑ ሊጠመቅ የሚችልበት መንገድ ቢኖር አጋጣሚ ብቻ ስለነበርና ሌላው አማራጭ ጀርመን/ኮሎኝ ሄዶ ክርስትና ማስነሳት አልያም እንደብዙዎቹ ሁሉ አቅራብያ ወደ ሚገኝ የግሪክ ቤተ ክርስቲያን መሄድም የሚሉትን ሁሉ ዳስሰን የተሻለ ብለን የመረጥነው ከሆላንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ካህን የሆኑትን አባት ወደ ዙሪክ ጋብዞ ዙሪክ ክርስትና ማስነሳት በሚለው ተስማምተን ቅዳሴው ለመጀመርያ ጊዜ ዙሪክ ውስጥ ተደረገና ሌሎች ሕጻናትም እንዲሁም የ 14 ዓመት ወጣት ክርስትና ተነሳች:: ይህ በራሱ የራሳችን የምንለው ቤተክርስቲያን ቢኖረን ልጆቻችን በስርአቱና በወቅቱ መጠመቅ ብቻ ሳይሆን ለመቁረብም ከዚያም በዘለለ የቤተ ክርስቲያን መኖር በማደግ ላይ የለውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ አማኞች ምን ያህል ሊጠቅም እንደሚችል ስለተገነዘብን በዙሪክ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን እንዲቋቋም ከመመኝትም በላይ መንገዶችን ማመቻቸት አለብን ብለን ወሰንን::

ጥያቄ: ከዚያስ?
አቶ ምሥጢረ: ከዚያ በኋላ የሆነው ሁሉ የእግዚአብሔር ተአምር ነው ብል ማጋነን እንዳይመስልብኝ እሰጋለሁ:: ቀጣዩ በሙሉ የእግዚአብሔር ተአምር ነው ማለቱ ብቻ የሚሻል ይመስለኛል::

ጥያቄ: ዘርዘር አድርገህ ብትገልጽልን?
አቶ ምሥጢረ: ሰፋ ሊል ይችላል:: እዚህ እኛ የምንኖርበት ቀበሌ ያለው የሪፎሮሚርት ፕሮቴስታንት ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ የሚያዘጋጀው የ"እንተዋወቅ" ፕሮግራም ነበር:: ያ ፕሮግራም በስደት: በሥራ ምክንያትና በሌሎችም ምክንያቶች አካባቢው ነዋሪ የሆኑ የተለያዩ እምነቶችና ባሕል ያላቸው ሕዝቦች በአንድ ላይ ተገናኝተው የቻለ የባሕል ምግብ ሰርቶ ይመጣና አንዱ የሌላውን እየቀመሰ የሚተዋወቅበት ቀን ነው ያ ቀን:: እኔና ትልቁ ልጄ ያሬድ በተከታታይ ተገኝተናል ብዙ ሰዎችም ተዋውቀንበታል:: በ2000 ዓ.ም. በነበረው ዝግጅት ላይ ግን አልተገኘንም:: ዘንግተነው ይመስለኛል:: ታድያ የዚያ ዝግጅት አስተባባሪ የሆኑት የሪፎርሚርተው ቄስ ማምሻውን ደውለው ለምን እንደቀረን: ብንመጣ ኖሮ አንድ ኢትዮጵያዊ የሆኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቄስም ማግኘት እንችል እነደነበረ ቄሱ ከእነ ባለቤታቸው በአቅራቢያችን ከሚገኘው የስደተኞች መኖርያ ውስጥ ነዋሪ ስለሆኑ ስልካቸውን ተቀብየላችኋለሁና ደውሉላቸው ብለው ስልካቸውን ይሰጡናል:: ደወልንላቸው በእውን ሥልጣን ያላቸው ቄስ መሆናቸውንና የመሳሰሉትንም ጠያይቀን ብንኝገናኝስ? ተባባልንና ቤት ውስጥ ያለነው ሁሉ ልናግኛቸው ወድያውኑ ሄደን:: ተገናኘን:: መስቀል አሳልመው አረፍ እንድል ጋብዘው ትንሽ ተጨዋወትንና ለጊዜው ወንጌል ለማስተማር ዝግጁ ነኝ ቦታ ከተገኘ የሚቀጥለው እሁድም ቢሆን ለእኔ መላካም ነው ስላሉን ተደስተን ተለያየን::
ቦታም እዚያው ረፎርሚርተ ቤተክርስቲያን ውስጥ ክፍል ተሰጠንና የምስራቹን እየደወለን በነገሩ ይደሰታሉ ብለን ላመንባቸው ሁሉ ነገርን:: እነሱም እንዲሁ ለሚያውቁት እንዲነግሩ ተስማምተን እሁድ ማርች 12 ቀን 2000 ዓ.ም. ለመጀመርያው ትምሕርት ተገናኘን::ያ እለት የመጀመርያው ቀን ሆነ ማለት ነው::


ጥያቄ: ያ ስብስብ ወደቤተ ክርስቲያንነት እንዴት አደገ? ስያሜውስ እንዴትና ማን ሰየመው?
ነሐሴ 2002 - ደብረ ገነት ቅድስት ድንግል ማርያም ኦፕፊኮን/ ዙሪክ 10ኛ ዓመት -ልዩ እትም 4
አቶ ምሥጢረ: ጥሩ ጥያቄ ነው:: ካህን ተገኘ! ለማገልገል ፍጹም ፈቃደኛ ናቸው:: ሌላ ሌላውን ማመቻቸቱ የእግዚአብሔር እርዳታ ከተጨመረበት የእኛ ፋንታ ነው የምንል ሰዎች ተሰባሰብንና ተወያየን:: ቦታ ማግኘቱ የመጀመርያው ሊሆን ይገባዋል ተብሎ ስለታመነበት ያ ሃላፊነት ለእኔ ተሰጠና ስናፈላልግ በመጀመርያ የተሰጠን የሪፎርሚርተው ቦታ ጠባብ በመሆኑ: ግቢ ጠባቂዎቹም እሁድ ገባ ወጣ ማለታችንን ስላልወደዱት አሁን ወደ አለንበት ቦታ እንድንሄድና ሃላፊዎቹን እንድናነጋግር ከቀበሌው አስተዳደር ተጠቁመን ካህኑን (ቀሲስ ፍቅረ ማርያም)ን ይዘን የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያኒቱን አስተዳዳሪ የሆኑትን ሰው አነጋገርን:: እሳቸውም እላይ ዋናው የነሱ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ግማሹን ከፍለን ለጸሎት ትጠቀሙበታላችሁ ብለው ነበር:: ያ ደግሞ ከስርዓታችን ጋር የማይመች ስለሚሆን ሌላ አማራጭ ካለ ብለን ጠይቀን የተገኘው አሁኑ ቤተ ክርስቲያናችን አድርገን የምንጠቀምበት ቦታ ብቻ ሆነ:: ክፍሉ የወጣቶች የመጫወቻ ክፍል በመሆኑ እነሱ ከሰዓት በኋላ 14 ሰዓት ስለሚገቡ እንደነበረ አድርጋችሁ ታስረክባላችሁ የሚል አማራጭ አገኘን:: አንዳንዶቻችን ያልወደድነው አማራጭ ቢሆንም "ቀሲስ ፍቅረ ማርያም" ስለወደዱት ወደዚያ ያሉንን በጣም ትንሽ እቃዎች አስገባን:: ቦታው የሚጨስበት ልዩ ልዩ ጨዋታዎች እንደ የጠረጴዛ ኳስና ከረንቦላ መጫወቻ ቦታ በመሆኑ የሲጋራውን ቁርጥራጭ ጠራርጎ:ጠረጴዛ እየጎተቱ ቦታ ማስያዝ መልሶ እንደነበረ ማድረግ በተለይም ቦታውን ቤተ ክርስቲያን ማስመሰል የዋዛ ሥራ አልነበረም::
ስያሜው ላይ "መድሃኔ ዓለም" ጄኔቫ ስላለ ሉዘርንም በእመቤታችን ስም አልፎ አልፎም ቢሆን ጸሎት ስለሚደረግ - ቅዱስ ሚካኤል - ቅዱስ ገብርኤል - ቅዱስ ጊዮርጊስ የሚሉት ሁሉ ተነስተው በይበልጥ በካህኑ የትም ቢኖር እዚህም የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሊባል ይችላል ብለው " ቅድስት ድንግል ማርያም" የሚለው ተመረጠ::
እንዲያ እንዲያ እያልን ቦታውም የወጣት ክፍል መሆኑ ቀረና ሙሉ በሙሉ (አልፎ አልፎ ለካቶሊክ ወጣቶች ጉዳይ ካልተፈለገ በስተቀር) እንድንጠቀምበት ሆነ:: በመጀመርያ ከጸሓዬ ጽድቅ መድሃኔዓለም (ጄኔቫ) ቤተ ክርስቲያን ንዋየ ቅድሳት እየተዋስንና ሌላ ሌላም ድጋፍ እየተደረገልን በአባቶች ሜሮን ከተቀባልን በኋላ ቅዳሴ እስከ መቀደስ ተደረሰ:: ውጣ ውረድ ግን ነበረው::
ጥያቄ: ያገጣማችሁ ችግር እንደነበር ሲወራ ሰምተናል:: ምን ነበር? ዋና ዋና ችግሮች ነበሩ ብለህ የምታምናቸው እንዴትስ ተቀረፉ?
አቶ ምሥጢረ: በመጀመርያ እኛ ከላይ ያልኩህን በጀመርንበት ጊዜ ለስዊስ ቋሚ ካህን ለማምጣት ተሞክሮ እንዳልተሳካ እንሰማ ነበርና እዚህ የእመቤታችን ቤተ ክርስቲያን መመስረት እርዳታ ያደርጋል ተብሎ ስለታመነበት ብቻ ሳይሆን በሌላ በሌላ ጉዳዮችም ላይ በጋራ መሥራት እንዳለብን እኛ አምነናል:: ጄኔቫ ከእኛ ቀደም ብሎ ከ 20 ዓመታት ላላነሰ ጊዜ በስዊዘርላንድ ውስጥ በብቸኝነት ለኢትዮጵያውያን ምዕመናን መንፈሳዊ አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው የጸሐየ ጽድቅ መድሃኔ ዓለም ጋር መነጋገር እንዳለብን ስላመንን ለምሳሌ በቅዳሴ ወቅት የሚጠራው የፓትርያርክ ስም ጉዳይና የመሳሰሉትን አንስተን በስዊዘርላንድ ውስጥ ያለው ምዕመን በምንም መልኩ በሌላው ዓለም ውስጥ የሚታየው መከፋፈል እንዳይኖር በየቤተክርስቲያናቱ በጥቅሉ ለጳጳሳቱ- ቀሳውስቱ-ምዕመኑ ከመጸለይ በስተቀር የህ የ እገሌ ነው ያ ደግሞ የእገሌ ነው መባል የለበትም የሚለውን አሳምነን ተቀባይነት አገኘ:: ያ ትልቁ ሊለያየን የሚችል መሰናክል ነበርና በ እግዚአብሔር ቸርነት አለፍነው:: ሌላው ከላይ በቤተ ክርስቲያናችን መቋቋም ላይ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርገዋል ያልኩህ ሰው ጉዳይ ነው:: ወንጌል በማስተማር በኩል ደህና ቢሆኑም ቅስናው ላይ ላይ እጅግም ናቸውና ክሕነታቸውም አጠራጣሪ ነው የሚለው ጉዳይ አብረን ለመቀጠል ስላላስቻለን መለያየት የግድ ሆነ:: እንግዲህ እንደምትገምተው በዚህ ሁኔታ መለያየቱ ቀላል ባለመሆኑ አንዳንድ ጠባሳዎች ለጊዜውም ቢሆን ጥሎ ማለፉ አልቀረም::
የዚያንኑ ያህል ድንቅ የሆኑ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች በየጊዜው የሚነሱ ችግሮችን በዘዴና በአርቆ አስተዋይነት ይልቁንም በጽኑ እምነት በመታነጻቸው አልፈናቸዋል::በዚያ ፈታኝ ወቅት የወንጌል ትምሕርት እንዳይቋረጥብን የተቻላቸውን ሁሉ በማድረግ የማይናቅ አገልግሎት ያበረከቱትን ዲያቆን መኮንን ግርማና ዲያቆን ዳንኤል ኃይሉን ማንሳት የግድ ይለኛል:: እዚህ ላይ የሰበካ ጉባኤና በሰንበት ትምሕርት ቤት ታልቅ አስተዋጽኦ ያደረጉትን ሁሉ በእመቤታችን ስም ምስጋና ለማቅረብ እወዳለሁ:: በተለይም በአሁኑ ጊዜ እዚህ ሀገር ከእኛ ጋር ባይሆኑም ዲያቆን መኮንን ግርማን: አቶ ሰናይ ምንውየለትን; ዶክተር
ነሐሴ 2002 - ደብረ ገነት ቅድስት ድንግል ማርያም ኦፕፊኮን/ ዙሪክ 10ኛ ዓመት -ልዩ እትም 5
ርብቃ ፍሥሐንና ዘማሪት ኤልሳ ኢብሳን ሳላነሳ ባልፍ ሕሊናየ እረፍት አያገኝምና መጥቀስ እወዳለሁ::

ጥያቄ: ቤተ ክርስቲያኒቱ ከሌሎች አብየተ ክርስቲያናት ጋር ያላት ግንኙነት በተለይም ስዊዘርላንድ ካሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያናት ጋር ያለው አንድነት ምን ይመስላል?
አቶ ምሥጢረ : በካንቶን ዙሪክ ካሉ አብየተ ክርስቲያናት ጋር በጣም ጥሩ ግንኙነት አለን:: ቀደም ሲል ገና ቤተ ክርስቲያናችንን ለማቋቋም በወሰነበት ጊዜ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሁሉ መልካም ግንኙነት በመመስረታችንም ነው እንዴት ለስዊዘርላንድ አንድ ቋሚ ካህን የሥራ ፈቃድ ሊያገኝ እንደሚችል ምክርና መመርያም ያገኘነው:: በስዊዘርላንድ የአብያተ ክርስቲያናቱ አባል ስንሆን በስዊዘርላንድ ያሉ የኦርቶዶክት ሕብረት (አምስቱ ኦርየንታልና ሩስያ- ሰርቭያ - ግሪክ -ሩማንያ)ሕብረት ለሁለተኛ ጊዜ ዋና ጸሐፊ ሆና ተመርጣ ቤተ ክርስቲያናችን በ ያሬድ ኃይለ ሥላሴ ጸሐፊነት የሥራ አስፈጸሚው አካል ናት::በዙሪኩ የአብያተ ክርስቲያናት አባልነታችንም በኩል ነው ሌላ የተሻለ ቤተ ክርስቲያን የማግኘት ተስፋ አድርገን የምንጠብቀው:: የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስን በሚመለከት በሀገር ስዊዘርላንድ እንዲስፋፋ ለሚደረገው ጥረት የበኩላችንን ከማድረግ ተቆጥበን አናውቅም:: የሰንበት ትምሕርት ቤቶች እንዲስፋፉ የባለሙያም ሆነ ቁሳቁሳዊ ድጋፍ አድርገናል እናደርጋለን:: ለምሳሌ በርን ቤተ ክርስቲያን ለማቋቋም በተደረገው ጥረት ቦታ እንዲያገኙ ለሚመለከተው ክፍል ደብዳቤ የጻፍነው እኛ ነን:: ከቤተ ክርስቲያኖቻችን አስተዳደሪ እንዲሁም ትልቅ ሥራ በመሥራት ላይ ካለው ከማእከላዊው የሰበካ ጉባኤ ጋር እጅግ በጣም ጥሩ ሊባል የሚችል ግንኙነት አለን::

ጥያቄ: ለወደፊቱስ ምን እቅድ አለ?
አቶ ምሥጢረ: የራሳችን የምንለው ቤተ ክርስቲያን በማፈላለግ ላይ ነን:: ፍላጎታችን ትንሽ ሰፋ አለና እስካሁን ለማግኘት ተቸገርን:: ከአንድም ሁለት ሶስት አግኝተን የተውናቸው አሉ:: እኛ እቃ ቤት ያስፈልገናል: ለብቻ ለጸበል ጸዲቅ መቅመሻ የሚሆን ቢቻል አዳራሽ አለበለዝያም ሰፋ ያለ ክፍል እንፈልጋለን:: በዓላታን ስናከብር በማኅሌትና በያሬዳዊ ወረቦችም ከበሮዎቻችንን እንደልባችን እየመታን እልልታው እንደልብ ቀልጦ ማክበሩን እንፈልጋለን ስለዚህም በቀላሉ የማይረበሽ ከመኖርያ ቤቶች ፈንጠር ያለ ቢሆን ይመረጣል:: ይህንን ሁሉ የሚያሟላልን ማግኘት ከባድ ነው:: አምላክ በተአምሩ የቆረቆራትን የእናቱ ስም የሚጠራባትን ቤተ ክርስቲያን እኛ ብናስብም እሱ ቀኑን ቆጥሮ እንደሚያሳካው እምነቴ ነው:: በሌላ በኩል ተጀምሮ የነበረው የአማርኛ ትምሕርት ቤት በቅርቡ ይቀጥላል ብለን አቅደናል:: ቤተ ክርስቲያን ፈልገው ለመጡ መንፈሳዊ አገልግሎት መስጠቱ የተለመደ ነው:: ወደ ፊት አቅም እንደፈቀደ እኛም ወጣ ብለን የጠፉትን ከቤተ ክርስቲያን የራቁትን ማምጣትም ይጠበቅብናልና በእቅድ ደረጃ አለ::

ጥያቄ: ለሰጠህን ማብራርያ እናመሰግናለን:: በመጨረሻ ለማስተላለፍ የምትፈልገው መልእክት ካለ?
አቶ ምሥጢረ: አዎን! ለዚህ ያደረሰንን አምላክ አመሰግናለሁ:: አስር ዓመት ብዙ ባይባልም የሚናቅ አይደለም::እክሎች; መሰናክሎች አልነበሩም ማለት አይደለም:: ካቶሊኮች አስጠግተውን: ፐሮቴስታንቶች ይህው ዛሬ አስረኛ በዓላችንን የምናከብርበትን ቦታ ሰጥተውን ሌሎች የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት እንኳን ደስ ያላችሁ እንኳን ለ አስረኛ ዓመት በአላችሁ በሰላም ያደረሳችሁ እያሉን ባሉበት ወቅት: በስሙ ክርስቲያን የተባልን የክርስትና እምነት ተከታዮች ሁሉ በሚቻለው ሁሉ ለመተባበር ስንሞክር በተቃራኒው ለመንጎድ የሚፈልጉትን ስናይ እና ስንሰማ ማዘናችን አልቀረም:: ቤተ መቅደስን ለመገንባት እግዚአብሔር ለፈቀደለት እንጂ እንደ ልቤ ለሚለው ለቅዱስ ዳዊት እንኳን አልሆነም:: እግዚአብሔር በመረጠው መንገድና ሰው ሁሉንም ነገር ያከናውናል:: የሕይወት ተመክሮየ እውነት ትመነምናለች እንጂ አትበጠስም የሚባለውን አባባል ከልቤ እንዳምን አድርጎኛል:: እውነት እንደሚያዋጣ በተደጋጋሚ አይቻለሁ:: ኖሬዋልሁ:: ትዕግሥት ከታከለበት የእውነት አምላክ እግዚአብሔር ካንተ ጋር ከሆነ የማይቻል የሚመስለው ሁሉ ይቻላል:: እውነት ታሸንፋለችና እንደምታየው ከመሃከላችን ለቤተ ክርስቲያናቸው ቀናኢ የሆኑትን አምላክ እያስነሳ ዛሬ ለቤተ ክርስቲያኒቱ እድገት የሚደረገው ርብርቦሽ በቀላሉ የሚታይ አይደለም:: ከውጭ የሚሰሙት እውስጥ ሆነው ከሚያዩት ጋር አልጣጣም እያላቸው እየታዘቡም እያዘኑም ነው:: ለቤተ ክርስቲያኒቱ እላይ ታች የሚሉ አገልጋዮችዋን እግዚአብሔር ይባርክ! ፍቅርና አንድነት ይስጠን::ከዚህ በላይ የምጨምረውም የለኝ ለተሰጠኝ እድል ከልቤ አመሰግናለሁ::